Friday, December 18, 2015

ጎዳናው የት ያደርሳል?



ተስፋዬ ገብረአብ (Gadaa)

አባይ ፀሃዬ ስልጣኑን ከመለስ ዜናዊ ከተረከበ ወዲህ የመጀመሪያው ከባድ ፈተና ገጥሞታል። ከሰላሳ ቀናት በፊት ጀልዱ ተባለች ትንሽ መንደር ላይ የተለኮሰው ቁጣ እና አመፅ መላ ኦሮሚያን አጥለቅልቆታል። ይህን ፅሁፍ ከማተሜ በፊትም አመፁ ከኦሮሚያ አልፎ ወደ ምእራብ ጎንደር የተስፋፋ ሲሆን፤ የወያኔ ቡድን የገጠመውን ፈተና በምን አይነት ዘዴ ማፈን እንደሚችል ሲመክር መሰንበቱ እውነት ነው። ይቻላቸው ይሆን? የሚቻልበትም ሆነ የማይቻልበት እድል አለ።

በምርጫ 97 ወያኔ ከመውደቅ ለጥቂት አምልጦአል። መለስ ዜናዊ አዲስአበባን ለቆ ቢሾፍቱ ላይ የማዘዣ ጣቢያውን ተክሎ ነበር። ይዛው ለመሸሽ ሄሊኮፕተር ሞተሯን ሳታጠፋ ትጠብቀው ነበር። ያ እድል በአንዳንድ ሰንካላ ምክንያቶች ከመሳካት ተደናቅፏል። የወያኔ ስርአት ከሽፍታነት ጠባዩ እንዲላቀቅ ለማስገደድ ይህ የሰሞኑ ህዝባዊ አመፅ ሌላው እድልና ወርቃማ ጊዜ ነው። በርግጥ እንዳጀማመሩ በኦሮሞ ህዝብ መስዋእትነት ብቻ ወያኔ ከስልጣኑ ቢወገድ ለኢትዮጵያ በጎ አይሆንም።  የኦሮሞ ህዝብ ያለማንም ድጋፍ የከፈለውን ያህል ከፍሎ ለመብት ጥያቄው ምላሽ ሊያገኝ ይችላል። ሂደቱ በዚህ መንገድ ከተጠናቀቀ ከዚያ በሁዋላ ኢትዮጵያ እንደ አገር የመቆም እድሏ አጠያያቂ ይሆናል። በዚህ አጋጣሚ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለመጪው ዘመን የሚጠቅም በጎ አስተዋፅኦ ማድረግ ከቻለ ግን ኢትዮጵያ ብቻ ሳትሆን አካባቢያችንም ከታላቅ ቀውስ ይድናል።

ይህችን እየፃፍኩ ሳለ 71ኛው ኦሮሞ የመገደሉን ዜና ሰምቻለሁ። እና አዝኛለሁ። በጣም አዝኛለሁ። ያዘንኩት 71 ኦሮሞዎች በመገደላቸው ብቻ አይደለም። በተያያዘ የብዙ ሺህ የሰው ህይወት ሊጠፋ ይችላል ብዬ በመስጋቴ ጭምር ነው። መቸም ቢሆን በከንቱ ፈሶ የሚቀር የሰው ልጅ ደም የለም። የህወሃት ጓደኛሞች በረጋ ህሊና ቆም ብለው እንዲያስቡ እመኛለሁ። ጊዜ አለው ለሁሉም። ጊዜ በራሱ ቀመር የራሱ ተገላቢጦሽ አለው። እየተገደሉ ያሉት ወጣቶች የሰው ልጆች እንጂ ከጭቃ የተሰሩ ጡቦች አይደሉም። እና የማንመኘው ዘመን እንዳይመጣ መስጋት ይገባል።

በርግጥ ጊዜው ደርሶአል። ‘ጊዜው የደረሰን አሳብ ማቆም አይቻልም።’ ይባላል። በአመፅ ላይ ያለውን የኦሮሞን ህዝብ ወይም በጥቅሉ የመብት ጥያቄ እያነሳ ያለውን ኢትዮጵያዊ ማፈንም ሆነ ገድሎ መጨረስ አይቻልም። ወያኔ ጊዜ በማራዘም፣ በማሰላቸት፣ ድብደባውን በማጠንከር፣ በገፍ በማሰር፣ ግድያውን በመጨመር አመፁን አዳክሞ የማቀዝቀዝን ስልት እየተጠቀመ ነው። የኦሮሞን ህዝብ የመብት ጥያቄ ወደ ብሄር ግጭት በመጠምዘዝ ለሚወስደው ርምጃ ምክንያት ለማግኘት እየሞከረ ነው። “ኦነግ ከመጣ ይፈጀሃል” በሚል የተለመደ ማስፈራሪያ በተለይ የአማራውን የህብረተሰብ ክፍል ከጎኑ ለማሰለፍ እየሞከረ ነው። ፕሮፌሰር መሳይ ከበደ ታህሳስ 15 2015 “Oromo Uprising: Danger and Opportunity” በሚል ርእስ ባስነበበው ፅሁፍ የኦሮሞን አመፅ መደገፍ ለኢትዮጵያ አንድነት አደጋ እንዳይኖረው ስጋቱን ገልፆአል። ይህን የመሰለ መሰረት አልባ ጥርጣሬ በአንድነት ሃይሎች ዘንድ ይደመጣል። ለመጥቀስ ያህል መሳይ ከበደ እንዲህ ብሏል፣
Oromo political leaders and activists, including those of the OLF, should openly state that the uprising is not only about Oromo land, Oromo peasants, and Oromia, but that it is also a democratic movement that includes and speaks for other ethnic groups as well. With few exceptions, the word “Ethiopia” is not mentioned even once in the numerous declarations made by Oromo leaders and activists. The Oromo leadership must understand that there is no point for other ethnic groups to rise and support the uprising if the whole concept of a common country is removed from the political horizon. Without unity, the removal presages chaos, which is enough to stifle the will to show solidarity with the Oromo revolt.

መሳይ ከበደ ስጋን ከማስነበ አንድ ቀን ቀደም ብሎ ግን OLF በለቀቀው መግለጫ እንዲህ ብሎ ነበር፣

 This cruel regime is able to commit all these crimes by dividing the people of Ethiopia. Now, time is an essence for all peoples in Ethiopia to stand firm with Oromo people who have been fighting the TPLF regime for freedom, democracy, justice and human rights. The Oromo struggle is a struggle for freedom, justice, equality and human rights. When Oromo people are free from TPLF regime, all people in Ethiopia will be free. We are also encouraged by the support and solidarity of different Ethiopian political & Civil Organizations against the massacre of Oromo students and farmers by the TPLF regime. Now!

The OLF calls upon all Ethiopian to join the Oromo people struggle for freedom, democracy, justice & human rights, and once for all to dismantle the genocidal regime of TPLF. To that effect , the OLF calls for all inclusive struggle that include all political parties and civil organizations that will enable the Peoples in Ethiopia to decide their destiny by establishing government of people , for people and by people in Ethiopia.

We also warn everybody to be vigilant against possible evil actions of the TPLF to instigate animosity in the country by destroying property and killing none Oromo’s and blaming on Oromo’s. The TPLF will do this to disrupt this genuine movement towards freedom, democracy, human rights and justice. The Ethiopian people should be aware of the motives of the TPLF as it has been doing for the last 24 years since it seized political power in Ethiopia. It is widely known that the Oromo people have no problem with other people of Ethiopian, except with the TPLF and the systems that have been killing them, disposing them from their lands, arresting them & torturing them.

 OLF 40 አመታት ታግሎ አንድ ወረዳ እንኳ አልያዘም” የሚለው የአንዳንድ ወገኖች ሽሙጥ እውነት አዘል ትረባ አልነበረም። የኦሮሞ ህዝብ ትግል ልብና አእምሮን ከጨቋኙ ስርአት ነፃ እያወጣ በመጨረሻ ይህን ህብረ ትግል፤ ይህን ማመን የማይቻል ሰላማዊ አመፅ ለማየት አስችሎናል። ከአባዱላ እና ከባጫ ደበሌ በቀር የOPDO አባላት ልባቸው ውስጥ ከማንኛውም ኦሮሞ ያልተለየ ተመሳሳይ ጥያቄ አለ። መጫና ቱለማ ማህበር የለኮሰው ጥያቄ በቦታው አለ። የኦሮሞ ህዝብ ነባር ጥያቄዎች ገና ምላሽ አላገኙም። ከአሊ ቢራ እስከ ሃጫሉ ሁንዴሳ፣ ከመረራ ጉዲና እስከ ዱጋሳ በከኮ የኦሮሞ ህዝብ መንፈስ አንድ መሆኑ እየታየ ነው። እነ አቦማ ምትኩ፣ እነ መገርሳ በሪ፣ እነ አባጢቂ ኢንሰርሞ፣ እነ ዶሪ በሪ ሃሞ፣ እነ ይገዙ በንቲ፣ እነ ጨጨብሳ፣ እነ ፋፋም ዶዮ፣ እነ ኢረና ቀጨሌ ህይወታቸውን የሰጡለት ትግል በመጨረሻ እዚህ ደረጃ ላይ ደርሶአል። እነ ባሮ ቱምሳ፣ እነ ማሞ መዘምር፣ የዚህ አመፅ መነሻ የሆነችው ጀልዱ ያፈራቻቸው እነ አለሙ ቂጤሳ ያነሱት ጥያቄ ዛሬ በሚሊዮኖች ተደግፎ ድምፃቸው እየተሰማ ነው። ማፈን አይቻልም። የመብት ጥያቄ ነው። የኦሮሞ ህዝብ በፖለቲካና በሃይማኖት ሳይለያይ በአንድ ድምፅ እየጠየቀ ያለውን የመብት ጥያቄ ማቃለል ለአካባቢያችን አደጋ አለው። ርግጥ ነው፤ የኦሮሞ ህዝብ ሲወለድ ጀምሮ አብሮት የመጣ መብቱን በጉልበቱ መንጭቆ የራሱ እስኪያደርገው ድረስ ማንም ቢሆን በችሮታ አይሰጠውም። የከፈለውን ያህል ከፍሎም መብትና ክብሩን ማስጠበቁ የማይቀር ነው። 

ዘመናችን ኦሮሞ ወጣት አንዲት ጥይት ሳይተኩስ ምን ማድረግ እንደሚችል ልምድ እና እውቀት አጊኝቷል። ያገኘው ልምድና እውቀት ሃያል መሳሪያ ነው። አመያ ላይ የአግአዚን ሬጅመንት ከበው ያርበደበዱት ወጣት ፈረሰኞችን አይተናል። ቆርጦ በገነፈለ ህዝብ ፊት የታጠቀ ወታደር እንደ አሪቲ ጉዝጓዝ ከመሆን በቀር ሊያደርግ የሚችለው ነገር የለም። አኖሌ ዋቆ እንዳለው፣ የህዝብን የቁጣ አይኖች የመቋቋም አቅም ያለው ባለጠመንጃ የለም። በዚህ በሶስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ የኦሮሞ ህዝብ የ71 ውድ ልጆቹን ህይወት ቢከፍልም ገዳዮቹ ላይ አፀፋዊ እርምጃ አልወሰደም። ስላልቻለ አይመስለኝም። ከገደሉበት በላይ መግደል እየቻለ እስካሁን ነፍስ አላጠፋም። መሞትን ያልፈራ መግደል እንደማይቸግረው ግልፅ ነው። እና በዚህ በሰሞኑ አመፅ ኦሮሞ ሲሞት እንጂ ሲገድል አልታየም። ይህ ታጋሽነት፣ ይህ ሰላማዊነት ወደ መራራ በቀልና ቁጣ ሊቀየር የሚችልበት እድል ግን አለ። ማስተዋል ይገባል። አለማስተዋል ለፀፀት ሊዳርግ ይችላል። 

ብርሃኑ ነጋ እና አምን ዘለቀ ሲናገሩ የሰነበቱትን ተከታትያለሁ። ባርኔጣዬን አንስቼላቸዋለሁ። አርበኞች ግንቦት7 ከኦሮሞ ህዝብ ትግል ጎን ለመቆም ያሳየውን ቁርጠኛነት ማክበር እና ማወቅ የሚገባ ይመስለኛል። ኢሳት ቴሌቪዠን የኦሮሞን ህዝብ አመፅና መስዋእትነት የራሱ ጉዳይ አድርጎ በመውሰዱ ሊመሰገን ይገባዋል። ሰማያዊ ፓርቲና መኢአድ ታክቲካዊ ሳይሆን ስታራቴጂያዊ ርምጃ መውሰድ መቻል አለባቸው። የኦሮሞን ህዝብ አመፅ ከልብ ደግፈው ማበር ከቻሉ ለአካባቢያችን መረጋጋት ጠቃሚ ውጤት ያመጣል። የተከፋፈለ ቤት ሲቆም አላየንም። በመጪው ዘመን በአንድ ጎጆም ሆነ በጉርብትና አብሮ መኖር የማይቀር ስለሆነ ስለነገ አጥብቆ ማሰብ ይገባል። በዚህ ወቅት ከኦሮሞ ህዝብ ጎን አለመቆም የኦሮሞ ህዝብ በኢትዮጵያዊነት ማእቀፍ ስር ለመኖር ያለውን ጥቂት ተስፋ መግደል መሆኑን የማይገነዘብ ፖለቲከኛ ኢትዮጵያን ወደ ገሃነ እሳት ለመጨመር እንደተባበረ ማወቅ አለበት። የማንመኘው አደጋ ከደረሰ ችግሩ የእያንዳንዱን ዜጋ ጎጆ ሊያንኳኳ ይችላል። የኦሮሞ ህዝብ የመብት ጥያቄዎች በሌሎች ኢትዮጵያውያንም ሲነሱ የቆዩ ናቸው።  ወያኔ እንደ ኢሰፓ ስርአት ተግባራዊ ያማያደርገውን አዋጅ፣ ፖሊሲና ድንጋጌ ሲያረቅና ሲያፀድቅ የኖረ ቡድን እንደመሆኑ ስርአቱን የመቀየር ጥያቄ ትግራይን ጨምሮ የመላ ኢትዮጵያውን ጥያቄ ሆኖ ቆይቷል። 

ሶስተኛ ሳምንቱን የያዘው የኦሮሞ ህዝብ አመፅ ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር ብቻ የተያያዘ አይደለም። በርግጥ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን መቃወም የአመፁ ቀዳሚ መፈክር ነው። ተያያዥ ጥያቄዎችም ግን በኦሮሞ ህዝብ ተቃውሞ ውስጥ እየተደመጡ ነው። “የፖለቲካ እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ይፈቱ!!” የሚለው ጥያቄም ዋና ነው። “በመሃመድ አላሙዲ ስም የሚካሄድ ዝርፊያ ያብቃ!!” ሌላው ጥያቄ ነው። የኦሮሞ ህዝብ ክልሉን ያለሞግዚት በራሱ ማስተዳደር ይፈልጋል። ይህም ቀዳሚ ጥያቄ ነው። Oromiyaan Haadursitu!! የሚል መፈክር መስማታችን ያለምክንያት አይደለም። ሲታፈንና ሲዳፈን ዘመናት ያስቆጠረው የመብት ጥያቄ ስርነቀል መፍትሄ ካላገኘ በጥገናዊ ለውጥ ጥያቄዎችን አፍኖ ማስቀረት የሚቻል አይደለም። የሚቻል የነበረበት ዘመን አልፎአል። እድሉም አምልጦአል።
 
ርግጥ ነው፤ የኦሮሞ ህዝብ የሚያነሳቸው ጥያቄዎች የመላ ኢትዮጵያ ህዝብ ጥያቄዎች ናቸው። በቤኒሻንጉል እና በጋምቤላ ጭቆናና አፈና አለ። በደቡብ ኢትዮጵያም እንዲሁ ጭቆናውን እየተቃወመ የሚሰዋ ዜጋ አለ። በትግራይ ህወሃትን የሚቃወሙ አማፅያን አሉ። እየታገሉ እየተሰው ነው። የወልቃይትና የአርማጭሆ ሚሊሻ የወያኔን አፋኝ ስርአት በመቃወም ጠመንጃውን እንዳነገበ ሰልፍ ወጥቶአል። በሰራዊቱ ውስጥ ጭምር የአመፅ እንቅስቃሴዎች አሉ። በጥቅሉ ዛሬ የኦሮሞ ህዝብ ህይወቱን እየከፈለላቸው ያሉ ጥያቄዎች የመላ ኢትዮጵያውያን ጥያቄዎች ናቸው። ተመስገን ደሳለኝ፣ እስክንድር ነጋ፣ አንዱአለም አራጌ፣ አንዳርጋቸው ፅጌ እና አብርሃ ደስታ ወደ ወያኔ ማጎሪያ የተወረወሩት መሰረታዊ የሆኑ የሰው ልጆች ዴሞክራሲያዊ እና ሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ በመጠየቃቸው ነው። “የአመለካከት ልዩነት አንድን ዜጋ እንዲሞት ወይም እንዲታሰር ሊያደርገው አይገባም” በማለታቸው በእስር ቤት ተቆልፎባቸዋል። አሊያም በተለያየ መንገድ እንዲሞቱ ተደርገዋል። ደበላ ጣፋ የገብረጉራቻ ልጅ ነው። ከዩንቬርሲቲ ትምህርቱ ታፍኖ ከተወሰደ በሁዋላ፣ አስር አመታት ታስሮ፣ ከሁለት አመታት በፊት ተፈትቶ ነበር። መንፈሱ ባለመሰበሩና ተቃውሞውን በመቀጠሉ ገድለው ሬሳውን መንገድ ላይ ጣሉት። በኦነግ አባልነታቸው በደርግ ጊዜ ታስረው የነበሩት ኦቦ ሰኚ ዛሬም ቃሊቲ እስር ቤት ሲሆኑ፣ በጥቅሉ የእስር ቤት ህይወታቸው ወደ ሰላሳ አመታት ተጠግቶአል። በመላ ኦሮሚያ የተቀሰቀሰው አመፅ የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ከመቃወም በላይ የመረረ ብሶት አምቆ የያዘ ነው። ከአቅሙ በላይ ተለጥጦ ሲያበቃ የፈነዳ አመፅ ነው። ሞት ወይም የመብቶች መከበርን በምሬት የሚጠይቅ ህዝባዊ አመፅ ነው።
    
መታወቅ ያለበት እውነት አለ። ገንፍሎ ያመፀው ህዝ መንፈሱን አዳክሞ ለጨቋኙ ስርአት የመረጋጋት እድል ከሰጠ አንገቱን ለወያኔ የበቀል ካራ አዘጋጀ ማለት ነው። ስርአት እየተለዋወጠ ሲበዘበዝ የኖረው ህዝብ የሙሉ መብቶቹን መከበር እስከያረጋግጥ በፅናት መታገል የተሻለ አማራጭ የለውም። በዚህ ወቅት ማፈግፈግ መሞት ማለት ነው። ትግሉ በቅንጅትና በፅናት መቀጠል ከቻለ የሽግግር መንግስት ማቋቋም ያስፈልግ ይሆናል። ብሄራዊ የእርቅ ጥያቄ ወቅታዊ ሊሆን ይችላል። ጥላቻን ከሚያራግቡ ንግግሮችና ፅሁፎች መታቀብ ይገባ ይሆናል። የትግራይ ህዝብ እንደማንኛውም ሌላው ኢትዮጵያዊ የስርአቱ ሰለባ መሆኑን ከልብ ማመንም ይገባል።

በመጨረሻ - ልጆቹን ለሰዋ ቤተሰብ እግዚአብሄር አምላክ መፅናናቱን ይስጥ። አላህ ይርዳን!!
 
Gadaa Ghebreab    www.tgindex.blogspot.com , ttgebreab@gmail.com   December 18, 2015 

3 comments:

Anonymous said...

Bravo ! Very very interesting points. Ethiopian students especially in Oromiya region and Amharas are started armed struggle in Gondar this truly jump start the overall fight for FREEDOM.it is a very profound Article about our beloved country Ethiopia !! God Bless Ethiopia !!! Thank you

Unknown said...

Victory to the mass thank you mr.Tesfaye for your enlightenment.

Unknown said...

Victory to the mass thank you mr.Tesfaye for your enlightenment.